From Forum

ጠበቃ ፍለጋ

እውነቱ ታወቀ | 26/01/2014

አባ ፍቅረ ሥላሴ በከተማ ያሉትን የጠበቃ ቢሮዎችን እያዳረሱ ነው - አዲስ ጠበቃ ፍለጋ። ብራቸውን የበላው “በሀገሪቱ አለ የለም የተባለው” የድሮው ጠበቃቸው እንደፈለጉት የሆነላቸው አይመስልም። ወደ ህግ መሄዱ አያዋጣዎትምና ነገርዎን እዚያው በሰላም ይጨርሱ ብሎ አሰናብቷቸው ከሆነስ - ማን ያውቃል?
እኔን የገረመኝ ከወዳጆቻቸው ሁሉ፣ ከወንጀል ግብረ አበራቸው ሳይቀር ተደብቀው ብቻቸውን በየጠበቃው ቢሮ መዞራቸው ነው። ወዳጃቸው “ሊቀመንበሩ” ምን ቅር የሚያሰኝ ነገር አገኙበትና ከሱ ተደብቀው ወደ ጠበቃ ሄዱ? የሚያስገርም ክስተት ነው። ከዘጠኝ ዓመታት በላይ በወንጀል ተባብረው ቤተ ክርስቲያናችንን ሙጥጥ አርገው ዘርፈዋል። አሁን የCRA ኦዲተር መጥቶ ገመናቸውን ሊገልጠው ሲሆን ላንድ ወር እንኳ እንዴት አብረው መቆየት ተሳናቸው? ችግር መጣ ሲባል ገና ከጅምሩ ተካካዱ።
ለነገሩማ መነኩሴው በNovember 3 ስብሰባ ላይ አስቀድመው ክደውታል። ያውም በሕዝብ ፊት። እሳቸው ምናቸው ሞኝ? “የምን ገዳም ነው የምታወራው? ገንዘቡ ለኔ በስጦታ የተበረከተልኝ ነው” ብለው ትልቁን ሰውየ በስብሰባ መሃል ጥላውን ገፈው ሚጢጢ አላሳከሉትም እንዴ? ያኔ አይደል መካካድ የተጀመረው። በስተመጨረሻ ይህ እንደሚደርስ ሁሉም ሰው አስቀድሞ አውቆት ነበር። “ሁሉንም የሠራው እሱ ነው፣ እሱ ነው ያሳሳተኝ” ብለው መነኩሴው “ሊቀ መንበሩን” አንድ ቀን እንደሚክዱት ሁሉም ሰው ገምቷል። እሱ ግን ውርደት ቀለቡ ስለሆነ ያንን ሃፍረት ተሸክሞ ስብሰባውን ቀጠለ። ይባስ ብሎም “አዎ እጃቸውን ጠምዝዘን ነው የሰጠናቸው” ብሎ እዚያው በዚያው ነፍስ እንዳላወቀ ሕጻን ቃሉን ቀይሮ ተናገረ። ያንን ለCRA ፈርሞ ያስገባውን ደብዳቤ እንደሆነ ቢጮህ፣ መፈክር ቢያዥጎደጉድ፣ እርር ድብን ቢል አይመለስ። ለመሆኑ ደብዳቤው ምን ዓይነት መዘዝ እንደሚያመጣበት ተገንዝቦት ይሆን? እንደኔስ ከሆነ እሱ ነበር ጠበቃ መያዝ የሚያስፈልገው።
መነኩሴው ግን የዋዛ አይደሉም። አሁን ደግሞ እሱን ትተው ብቻቸውን ጠበቃ ፍለጋ ተሰማርተዋል። ይህ ድጋሚ ክህደት አይባልም? ነገሩ ራስህን አድን መሆኑ ነው። “እሱ ነው ፈርሞ የሰጠኝ እንጂ እኔ ምኑን አውቄው፣ እኔ ለራሴ ምስኪን መነኩሴ፣ ላገሩ እንግዳ፣ ቋንቋውን አላውቅ” ብለው እሱን አጋፍጠው ለማምለጥ ስለፈለጉ ነው አይደል ከሱ ኋላ ተደብቀው ጠበቃ የሚያማክሩት? ጥሩ ሙከራ ነው። ግን ተሳስተዋል።
ገንዘቡን በተመለከተ ከምዕመናን ቢጠየቁ “ይህንን ሕዝብ የሰበሰብኩት እኮ እኔ ነኝ። እንደሰበሰብኩት ሁሉ ብፈልግ በሁለት ቃል እበታትነዋለሁ” ብለው ፎክረው እንደነበርም ሰምተናል። እዚህ ላይ አንድ ነገር መገንዘብ ይኖርባቸዋል። ሰብሳቢው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። እርሱም በስሙ መንጋውን እንዲሰበስቡ እንጂ እንዲበትኑ አልፈቀደልዎትም። መበተን የዲያብሎስ ሥራ መሆኑን አይዘንጉት።
እንዴት ዓይነት ጭካኔ ነው? ያ ለራሱ ሳይደላው እርሳቸውን ሲንከባከብ የኖረውን የዋሁን የዊኒፔግን ሕዝብ እርስ በርስ ሊያፋጁት ማቀዳቸው ገና ሳስበው ይዘገንነኛል። እግዚአብሔር በቸርነቱ ጠብቆን እንጂ በOctober 27 ስብሰባ ዊኒፔግ ዩኒቨርስቲ የነበረውን ሁኔታ የተመለከተ ሰው መነኩሴው ያቀዱት ደረሰ ሳይል ይቀራል? እሳቸው የፈለጉትን ካላሳኩ ሌላው መፋጀት አለበት? እስቲ ሕዝቡ ምን በደላቸው? ሕዝቡን አፋጅተውስ እሳቸው የት ያመልጡ ይሆን?
እግዚአብሔርስ ይህንን ሁሉ ግፍ እያየ እንዴት ዝም ይላል? በጣም የሚያስገርሙ ሰው ናቸው። የማሳመን ችሎታቸው የሚያገርም ነው።
መነኩሴው ለጠብና ለሁከት ስንቱን የዋህ መልምለው አልነበር። አሁን ግን ያ መሰሪ እቅዳቸው አፈር ድሜ ስለበላባቸውና ሌላ አማራጭም ስለጠፋ በየጠበቃው ቢሮ መዞር ጀመሩ። ድሮ ጀምረውት ከነበረው ሕዝቡን የማባላትና የማናከስ እቅዳቸው ሁሉ የተሻለው፣ ቢከፋም ቢለማም፣ ወደ ህግ መቅረብ ነውና በበኩሌ ጠበቃ ማማከራቸውን ወድጀላቸዋለሁ።
ያም ሆነ ይህ January 21, 3፡00 pm ላይ TD Centre 22ኛ ፎቅ ወደሚገኘው የጠበቃ ቢሮ ብቅ ብለው ምክር ጠይቀዋል። ግን ምን ያደርጋል። የያዙት የተበላሸ ጉዳይ ከመሆኑና ቋንቋም ካለማወቃቸው ጋር ተደማምሮ ሁኔታው ውስብስብ ብሎባቸው፣ ያሰቡትን ሳይፈጽሙ ያንድ ቀን ስህተት የብዙ ዘመን ጸጸት ሆኖባቸው፣ ያችን $65 ሺ የተቀበሉባትን ቀንና አመቻችቶ የሰጣቸውን “ሊቀመንበሩን” እየረገሙ ቅስማቸው ተሰብሮ ተመልሰዋል። ወይ መከራ።
እኚህ ሰው ምነው እቅጩን ነግሮ ከገደል አፋፍ የሚመልሳቸው ሁነኛ ክርስትያን ወይ እስላም ወይ የኢሰፓ ካድሬ ወይ ወያኔ ወዳጅ አጡ? ለነገሩ ወዳጅስ ቢሆን በደህና ጊዜ ያላኖሩት አሁን ከየት ይመጣል? የነበሯቸው የልብ ወዳጆችም December 22 በኮሚኒቲ አዳራሽ ተሰባስበው የቻሉትን ያህል ለWinnipeg Free Press ዘጋቢ ነግረውላቸው ነበር። ሪፖርተሯ ናት ጉድ የሠራቻቸው። የተነገራትን ትታ ስለ ጠፋው ገንዘብና ስላወጡት አምባገነናዊ ሕግ ደጋግማ እያስረገጠች ወንጀለኛነታቸውን ላልሰማው አሰማችባቸው። ወያኔ ትሆን እንዴ? ለመሆኑ ማን አባቱ ነው ምንም ላትጠቅማቸው ዘጋቢዋን እናናግርልዎት ያላቸው? ክፉ፣ የክፋትና የጥፋት አማካሪ። እሳቸው የጠበቁት “ይህንን መነኩሴ የመሰለ ቅዱስ ሰው በዚህ ዓለም ላይ ፈጽሞ አልታየም፣ ለወደፊቱም አይፈጠርም” እያልች አሞጋግሳ እንድትጽፍላቸው ነበር። አልሆነም። ወይ ነዶ!
ደግነቱ ሦስተኛው ዙር ዘገባዋ ምን እንደሚመስል አይታወቅምና እንዲሁ በተስፋ መጠባበቁ ሳይሻል አይቀርም። ማን ያውቃል “የሊቀመንበሩ” ከፍተኛ ብልሃት የተሞላበት የመዝገብ አያያዝ ችሎታ CRAን ግራ አጋብቶ “ኦዲት ተደርገው ነጻ ሆነዋል” ያሰኘው ይሆናል።
የተበላሸ ነገር ይዘው በየጠበቃው ቢሮ እየሄዱ ደጅ ቢጠኑ ውጤት የለውም። ትርፉ እሳቸው ራሳቸው ሥራ ፈትተው ባለሙያዎቹን ሥራ ማስፈታት ነው። ለነገሩ እሳቸው እጃቸውን አለስልሰው ሳምንቱን ሙሉ ቀንና ሌሊት ስልክ እየደውሉ ሰውን ከማናከስ ሌላ ምን ሥራ ሠርተው ያውቁና? በየቀኑ በየጠበቃው ቢሮ ከመዞር የቤተ ክርስቲያናችንን ደጀ ሰላም ከፍተው ምዕመናኑ ባመቻቸው ሰዓት እየመጡ እንዲጸልዩ ቢፈቅዱላቸው አይሻልም ኑሯል? እርሳቸው እንደሆነ የተባረከ ምክር አይሰሙ። ምን በወጣቸው? ቤተ ክርስቲያንን በሳምንት ከሁለት ሰዓታት በላይ መክፈት የስልክና የወሬ ጊዜያቸውን ስለሚሻማባቸው አያደርጉትም። ስለዚህም አንድ እሁድ፣ ያውም ለሁለት ሰዓታት ከከፈቱት ይበቃቸዋል። እኔን ሁሌ የሚገርመኝ ግን፣ እኚህ ሰው በሳምንት ሁለት ሰዓታት ብቻ እየሠሩ ያንን የመሰለ ሰማይ ጠቀስ ህንጻ ውስጥ የሚኖሩት ደመወዛቸው ስንት ቢሆን ነው? ምነው ታዲያ ሌላው በሳምንት 50ና 60 ሰዓታት እየሠራ ኑሮ አልሟላልህ አለው? እንዲሁ ለወሬ ካልሞትኩ ብየ እንጂ በቅርቡ እምዬ CRA የተደበቀውን ምስጢራቸውን ሁሉ ጎልጉሎ ያወጣው የለ!
ለካ ልባቸው ወደ ጠበቃ ሂዶ ነው ሰሞኑን የቀን ቅዠት ውስጥ የገቡት? አንዳንዴማ የሚያናግራቸውን ሰውና ያሉበትን ቦታ ሁሉ መርሳት ጀምረዋል። በቂ እንቅልፍም የሚያገኙ
አይመስሉም። መቼ አወቅንላቸው? ላስተምራችሁ የሚሉን የወንጌል ቃልስ በርሳቸው ላይ ይሠራል ይሆን ወይስ እርሳቸው ወደ መላዕክት ቀረብ ስላሉ ትምህርቱ ለሌሎቻችን ነው?
አባ ጠበቆቹ እንደሆነ እንደ ሐረር ማሽላ ጥርሳቸውን ብልጭ እያደረጉ ገንዘብዎትን (ይቅርታ የቤተ ክርስትያናችንን ገንዘብ ማለቴ ነው) ያራግፉዎታል።
እኔ ልንገረዎት በከተማው ያሉት ጠበቆች ሁሉ በWinnipeg Free Press የወጣውን ታሪክዎን አንብበውታል። ስለዚህም ይህንን የማያውቅ ጠበቃ አገኛለሁ ብሎ ማሰብ ከንቱ ልፋት ነው። ደግሞም ባላጋራዎ CRA መሆኑን አይርሱት።
ያገሩን ጠበቃ ሁሉ ቢያዳርሱ ውጤቱ ተመሳሳይ ነው። ያገሪቱን ሕግ ለመሻር የሚተባበርዎ የለምና ተስፋ ይቁረጡ።
እኔ ልጠቁምዎ - እጅግ በጣም ጎበዝ ጠበቃ አለ። ከገቡበት ማጥ ውስጥ በቅጽበት ሊያወጣዎ የሚችል ብርቱ ጠበቃ!! ምንም ቢሆን ምን ተሸንፎ የማያውቅ ጠበቃ!! ሊያገኙት ፈቃደኛ ከሆኑ የት ማን መሆኑን እነግረዎታለሁ። ብቻ ይህ ጠበቃ የጠራ እውነትና ከልብ የመነጨ ንጹህ እንባ ይፈልጋል። እያስመሰሉ ከመኖር ያደረሱትን በደል ሁሉ ምንም ሳይደብቁ ዘርዝረውና ተንበርክከው ከልብ እያለቀሱ ለዚያ ጠበቃ ይንገሩት። ታዲያ ከልብ መሆን አለበት። ጥብቅናው ፍቱን ነውና ከዚህ ከተዘፈቁበት ጣጣ ያወጣዎታል። በኔ ይሁንብዎት፡ ይሞክሩት።
እሱም፣ እኛን ለማዳን ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው፣ የዓለሙ ሁሉ መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።

 
 

Re: ጠበቃ ፍለጋ

ዞሮ ዞሮ ስሩ አንድ ነው | 26/01/2014

አዎ ምህረቱ እና ቸርነቱ የማያልቅበት አምላክ ጥሩ ጠበቃ ነው! ዳኝነቱም የማያዳላ ነው! ወዳጆቼ ለምን አንመካከርም? ለምን ይቅር አንባባልም? መቼም ሰው ሆኖ የማያጠፋ የለምና ለምን በዲያብሎስ እጅ እንወድቃለን? አረ እንደው እባካችሁ እናስተውል። እንፈቃቀር፥እንከባበር የሰው ልጅ መከባበር እና መፈቃቀር ካለው በፍፁም ጠላታችን ዲያብሎስ ቦታ የለውም:: በኛ መለያየት እና መጣላት እሱ ይስቅብናል ለምን ግን? ምነው ማስተዋል ከኛ ተሰወረ? መለያየቱን ትተን በ አባታችን በመድሃኒአለም ጥላ ስር እንሰባሰብ:: አማራ፥ትግሬ፥ኦሮሞ፥ወላይታ፥ጉራጌ ሁሉም እንዲሁም የሀሳብ ወይም የፖለቲካ ልዩነት ያላቸው በሙሉ አንዱ አንዱን ያክብር ያዳምጥ:: ዞሮ ዞሮ መግቢያችን አንድናትና ምን አባላን? በማናውቀው ሀገር መጥተን ባህሉን ቋንቋውን ለማወቅ መከራ እናይ የለ ታድያ እርስ በራሳችን እንዳንፈቃቀር፥እንዳንማማር፥እንዳንከባበር ምን አይነት በሽታ ያዘን? እስቲ ክርስትያኖች እባካችሁ ሁላችንም በያለንበት ስለ ሀጥያታችን እየተጸጸትን እናንባ፥እንጸልይ መልሱ ፈጣን የሆነው አባታችን መልሱ ፈጣን ነው:: በራሄል እንባ እስራኤላውያንን ከባርነት ያወጣ ለኛም የ ሀጥያታችንን ማመዘን ሳያይ ከውስጣችን በአንድ በተባረከ ሰው እንባ አምላካችን ሰላማችንን ይሰጠናል። የእመቤታችን ጸሎት የመላዕክቱ እርዳታ አይለየን።